በክልላችን የሚገኙ 48 ወረዳዎችን ታላሚ ያደረገውና ከ1.2 ሚሊዮን በላይ ዜጎች መድኃኒት የሚያገኙበት የማህበረሰብ አቀፍ የጤና ዘመቻ በይፋ መጀመሩን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታውቋል።
የጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊና የቢሮ ሀላፊ ተወካይ አቶ ኃይሌ ዘውዴ ዘመቻውን አስመልክተው በሰጡት መግለጫ፤ “ህብረተሰቡን ለጤናና ለማህበራዊ ጉዳት የሚዳርጉ የአንጀት ጥገኛ ትላትሎችን ለማጥፋት የሚሰጠው መድኃኒት ውጤታማ እንዲሆን የሁሉንም አካላት ቅንጅታዊ ስራ ይጠይቃል” ብለዋል።
አቶ ሀይሌ አክለውም በተጨማሪም በዚህ ዘመቻ ከመድኃኒት እደላው ባለፈ ሌሎች ወሳኝ የጤና ተግባራት ተካተው እንደሚከናወኑ ገልጸዋል።
የበሽታዎች መከላከልና ጤና ማጎልበት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር እንዳለ ሳህሌ በበኩላቸው፤ “ዘመቻው በአለም ጤና ድርጅት መስፈርት መሰረት የበሽታው ስርጭት ጫና ከፍተኛና መካከለኛ በሆነባቸው 48 ወረዳዎች ለ10 ተከታታይ ቀናት ይካሄዳል” ብለዋል።
በዘመቻው የጸረ-አንጀት ጥገኛ ትላትሎች መድኃኒት እደላ፤ የቲቢ፣ የከፍተኛ ደም ግፊትና የዓይን ችግሮች ልየታ፤ የስነ-ምግብ ችግር ልየታና የማህፀን ጫፍ ካንሰር መከላከያ ክትባት፤ እንዲሁም የወባ መከላከልና መቆጣጠር ስራዎች በቅንጅት እንደሚሰሩም አብራርተዋል።
ዘመቻው ለ10 ተከታታይ ቀናት የሚቆይ ሲሆን ሁሉም ባለድርሻ አካላት ለዘመቻው ስኬታማነት አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል።




